በሱዳን በረሃ ተጉዘው የሰሐራን በረሐ እንደ ግመል ያቋርጣሉ፡፡ ረሃቡ፣ ጥማቱ በትግል እና በወኔ ይታለፋል፡፡
በየመንገዱ መኪና ሲበላሽ መቆሙ፣ ከፖሊሶች ለመደበቅ በየተራራው ሥር ከአንድ ቀን እስከ ለሁለት ሳምንት ያለ ምግብ መቀመጡ፤ በየቀኑ ብር ጨምሩ ከሚሉ አሻጋሪዎች ጋር መጨቃጨቁ የታለፍና ሊቢያ ይገባል፡፡
ከሊቢያ ፖሊሶች ተደብቆ፤ በማይታወቅ ቤት ውስጥ ከርሞ፣ በሌሊት ጀልባ ላይ ወጥቶ በሜዲትራንያን ባሕር ላይ ጉዞ ይጀመራል፡፡ በሕይወት እና በሞት መካከል እየተጓዙ፣ ከተሰበረ ኮምፓስ ጋር እየታገሉ፤ ልምድ በሌለው ካፒቴን እየተመሩ፤ በእግዚአብሔር ቸርነት ከባሕር አውሬ ተርፎ ማልታ ይገባል፡፡
ማልታ ላይ ደግሞ በፖሊስ ተይዞ መጀመርያ ወደ እሥር ቤት detention center ከዓመት እና ከሁለት ዓመት በኋላ ሲወጡ ደግሞ ወደ መጠለያ የድንኳን ካምፕ ይገባል፡፡ እሥር ቤቱ ዙርያው በግንብ እና በሽቦ የታጠረ ሲሆን አንዳንዶች እየዘለሉ፣ ሌሎች ዘመናቸውን ጨርሰው ወጥተው በአሁኑ ጊዜ ምንም አበሻ በውስጡ የለበትም፡፡
የመጠለያ ጣቢያው ውስጡ በኮንቴይነር እና በአረጁ ድንኳኖች የተሞላ ነው፡፡ ኮንቴይነሮቹ በቅርብ እንደመጡ ሰምቻለሁ፡፡ ድንኳኖቹ ግን ራሳቸው እርጅናቸውን ይመሰክራሉ፡፡ በተለይም በዚህ ያረጀ ድንኳን ውስጥ አጥንት ድረስ በሚገባውና ያገሬ ብርድ ማረኝ በሚያሰኘው የማልታ የክረምቱ ብርድ እንዴት ሆኖ ሊኖርበት እንደ ሚችል መድኃኔዓለም ይወቅ፡፡
በአሁኑ ጊዜ እዚህ መጠለያ የሚኖር አበሻ የለም፡፡ ሁሉም ጥለውት ወጥተው በየሥራቸው ተሠማርተዋል፡፡ እኔ ግን የታሪካችን አካል ነውና በቪዲዮ እና ፎቶ አስቀርቼዋለሁ፡፡
እንዲህ ተሰቃይተው እና መከራ ተቀብለው እዚህ ማልታ የደረሱት ሁሉ በአንድ ነገር ያስገርሙኛል፡፡ ሁሉም ለወላጆቻቸው እና ለእኅት ወንድሞቻቸው ያስባሉ፡፡ እነርሱ ያዩትን መከራ ሳያዩ እዚያው በሀገራቸው ሊረዷቸው ደፋ ቀና ይላሉ፡፡ እንዲህ በመከራ ደርሰው ለቤተሰቦቻቸው ገንዘብ ይልካሉ፡፡
ከዚህ በላይ ምን ደግነት አለ? የሚልኩት ገንዘብ እኮ የላብ ሳይሆን የደም ዋጋ ነው፡፡
Link to this comment:
All Comments (0)